የኢትዮጵያ መሪዎችና
የክብር ዲግሪዎቻቸው!
በሰሎሞን ተሰማ ጂ. semnaworeq.blogspot.com

ከደስታ ተክለ ወልድ ብያኔ ውስጥ ሁለት ቁም ነገሮችን ማውጣት እንችላለን፡፡ አንደኛ፣ “የተሾመ፣ ባለማዕረግ፣ ታላቅ
ሰው” የሚለው ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ፣ “በአእምሮ ለከበረ፣ ጨዋ ሰው ኹሉ” ባለክብር የመሆን ማዕረግና
ዲግሪ ይገባዋል ለማለት ነው የሞከሩት፡፡ በዚህ ሃተታ ውስጥ ሌላው አሻሚ ቃል “ጨዋ” የሚለው ነው፡፡ በገጽ 600 እና 601 ላይ
ሁለት የሚቃረኑ ትርጉሞችን ሰጥተዋል፡፡ የመጀመሪያው፣ “ጨዋ - ፊደል ያልቆጠረ፣ ያልተማረ፣ መኃይምን” ማለት ነው ይሉናል፡፡ የሁለተኛውን
ግን ፍጹም “ዐዋቂ፣ ዐዛውንት፣ ሽማግሌ፣ አስታራቂ፣ ገላጋይ” ማለት ነው እያሉ ይፈቱታል፡፡ በተጨማሪም፣ ጨው ምግብን ኹሉ እንደሚያስማማ፣ ጨዋም መክሮና ዘክሮ “አንተም ተው! አንተም
ተው!” ብሎ የተጣላን ያስታርቃል፤ በጠብ የተለያየውን በፍቅር አንድ ያደርጋልና፤ ስለዚህም ጨው እንደማለት ጨዋ ተባለ፡፡ ክርስቶስ
ደቀ መዛሙርቱን “እናንተ የምድር ጨው ናችሁ!” እንዳለው፡፡ “ጨው”ና
“ጨዋ” ተወራራሾች ሆኑ፤” እያሉ ያብራሩታል፡፡
ዋናው ቁም ነገር፣ ጨዋነትና ክብር ከአዋቂነትና ከአስታራቂነት ጋር የመያያዙ ጉዳይ ነው፡፡ የበር መዝጊያን ከውስጥና
ከውጭ እንደማየት ማለት ነው፡፡ መዝጊያነቱ አይለወጥም፡፡ (የጥንት ሮማውያን ለዋነኛው አምላካቸው የሰጡት ስያሜ ነው፡፡ “ጃኑስ”
ብለውት ነበር፡፡ ከጃኑስም ተነስተው “ጃኑዋሪ” ወይም የአሮጌው አመታቸውና የአዲሱ ዓመታቸው መዝጊያና መክፈቻ በር ነህ አሉት፡፡)
ዐዋቂነትና አስታራቂነት፣ ሽማግሌነትና ገላጋይነት ማለት ልክ እንደበር መዝጊያነት ያሉ ሁለት ገጾችና እጅግ የተቀራረቡ አንድነቶች
ናቸው::

በመቀጠልም፣ በብሔራዊ ቤተ-መንግስት በተከናወነው በዚሁ ሥነ-ሥርዓት ላይ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የሰላም ሽልማቱን የሰጡት
የዓለም ዓቀፉ የሰላም ሽልማት ካውንስል ዳኞች ሊቀመንበር ዶ/ር ሀንሚን ሱ ሲሆኑ - የክብር ዶክትሬቱን ደግሞ የሀናም ዩኒቨርሲቲ
ፕሬዝዳንት ዶ/ር ዩን ፕየሺን ናቸው፡፡ በሽልማት ሥነ-ሥርዓቱም ወቅት አቶ መለስ በሦስት አበይት ጉዳዮች ላይ ንግግር አደረጉ፡፡
እንደዚህ ሲሉ ነበር የጀመሩት፣ “የካውንስሉ ውሳኔ ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ የሀይማኖት መቻቻልና ተሰባስቦ ባንድ የመኖር ወርቃማ
ባሕል እንዳላት ያመለከተ ነው፡፡” ካሉ በኋላ፣ “ካውንስሉ - የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት መገንዘቡን ያሳያል፤”
አሉ፡፡ በመጨረሻም፣ “ሽልማቱ እንደ ሀገርና ሕዝብ በአካባቢው ሕዝቦች መካከልና በአሁጉሪቱ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍንና ወንድማማችነት
እንዲያብብ ለምናደርጋቸው እንቅስቃሴዎች መበረታቻ የሚሆን ነው፤” ነበር ያሉት፡፡
አዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዳተተው ከሆነ፣ “በሥነ-ሥርዓቱ
ላይ ፕሬዝዳንት ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ፣ ቄስ ዶ/ር ባምሁዋን ኪም-የሀናም ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሊቀመንበር፣ ሚኒስትሮች፣ ከፍተኛ የመንግስት
ባለስልጣናት፣ ዲፕሎማቶችና ታዋቂ ግለሰቦችም ተገኝተዋል፤” እያለ ይቀጥላል፡፡...... ተጠቃሹ (ሌላው) የአቶ መለስ ሽልማት በሕዳር/ጥር
1998 ዓ.ም ያገኙት የግማሽ ሚሊዮን የኖርዌይ ክሩነርና የክብር
ዲፕሎማቸው ነው፡፡ ሸላሚው ድርጅት “ያራ” የሚባል የማዳበሪያ (የፍግ) አምራችና ሻጭ ድርጅት እንደሆነም ታውቋል፡፡
ከአቶ መለስ ዜናዊ የሃያ አንድ ዓመታት አገዛዝ በፊት፣ ኢትዮጵያን በስመ አንድነት የገዙት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለ ማርያም
ናቸው፡፡ በሀገር ውስጥ ስማቸውን እጅግ አስረዝመው “ጓድ መንግስቱ ኃይለ ማርያም የኢሕድሪ ፕሬዝዳንት፣ የኢሠፓ ዋና ፀሐፊ፣ የአብዮታዊት
ኢትዮጵያ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥና የደርጉ ሊቀመንበር፣ ... ምንትስ” የሚል አታካች የቅጽሎች ጋጋታ ቢሸከሙም ቅሉ፤ አንድም
የሀገር ውስጥም ሆነ የውጭ አገር ዩኒቨርሲቲ የክብር ዲግሪ አልተሰጣቸውም፡፡ ሰውዬው መንግስቱ፣ በበጎ ጎን የሚነሱም ከሆነ እንኳን፣
“መንጌ ሀገር ወዳድ ወቴ ናቸው” ተብለው እንጂ “የተከበሩ-ባለማዕረግና ታላቅ ሰው ነበሩ” የሚል አንድም ኢትዮጵያዊ አላጋጠመኝም፡፡
“ቆራጡ መሪ፣ ጓድ መንግስቱ ኃይለ ማርያም የኢትዮጵያን ሕዝብ እጅግ ይወዳሉ” እያሉ ፕሮፓጋንዲስቶቹ እነሽመልስ ማዘንጊያ የባጥ
የቆጡን “በሠርቶ አደር” ጋዜጣቸው ቢለፍፉላቸውም፤ ሕዝብንና አገርን ጠልተውና በወፍራሙ ጥላቻቸው ሰበብም በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችንና
ዜጎችን ገድለውና አስገድለው ያለምንም የክብር ዲግሪ ወደሐራሬያቸው መረሹ፡፡ ወዳጄ ዳሪዎስ ሞዲ በሬዲዮ ዜና እወጃው እንዳነበበው፣
“ግንቦት 13 ቀን 1983 ዓ.ም አገር ጥለው ፈረጠጡ!” ወይም ደግሞ “ፈረጠጠ!” ከዚህ ያለፈ ይክብር ዲግሪ አልተሰጣቸውም፡፡
እስቲ ደግሞ፣ ስለግርማዊ ጃንሆይ፣ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴና የክብር ዲግሪዎቻቸው እናንሳ፡፡ የዛሬይቱ ኢትዮጵያ በሐምሌ 17 ቀን 1957 ዓ.ም እንዳተተው ከሆነ፣ጃንሆይ
እስከ ሐምሌ 1957 ዓ.ም ድረስ ብቻ እንኳን አስራ ስምንት (18) የክብር ዲግሪዎችን ተቀብለዋል፡፡ ከሐምሌ 1957 ዓ.ም በኋላም
ሦስት የክበር ዲግሪዎችን ጨምረው ሃያ አንድ አድርሰዋቸዋል፡፡ የሚደንቀው የመጀመሪያውን የክብር ዲግሪያቸውን ሲቀበሉ ገና የሠላሳ
ሁለት ዓመት ወጣትና የኢትዮጵያ መንግስት አልጋ ወራሽ ነበሩ፡፡ የመጨረሻውን (21ኛውን) የክብር ዲግሪያቸውን ሲቀበሉም ሰማኒያ
ዓመት ሞልቷቸው ነበር፡፡
በግንቦት 30 ቀን 1961 ዓ.ም የወጣው አዲስ ዘመን
ጋዜጣ እንዳተተው ከሆነ፣ “ግርማዊ ጃንሆይ የዳግ ሐመር ሾልድ
ሽልማት” ተሰጣቸው የሚል ዜና በፊት ገጹ ላይ አስፍሯል፡፡ በማስከተልም፣ አሶሺየትድ ፕሬስን ጠቅሶ፣ “ጃንሆይ በዓለም
ጉዳዮች ላይ ስለፈጸሟቸው ድንቅ ተግባሮችና በመላው ዓለም ስላቸው ከፍተኛ ተቀባይነት፣ የዚህ ዓመት የዳግ ሐመር ሾልድ ሽልማት ተሰጣቸው፤”
የሚል ሃተታ አስነብቧል፡፡
የጃንሆይን የክብር ዲግሪዎች ዝርዝርም እንደሚከተለው እናገኛቸዋለን፡፡ ከላይ በገለጽነው የዛሬይቱ
ኢትዮጵያ ጋዜጣ (የ13ኛ አመት፣ ቁጥር-35) አንባቢያን በገጽ 1፣ 3 እና 7 ላይ መመልከት እንደሚችሉ ለማስታወስ
እወዳለሁ፡፡
1ኛ. ከካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ - የሕግ የክብር ዶክትሬት
ዲግሪ ሲሆን በሐምሌ 1916 ዓ.ም አውሮፓን አልጋ ወራሽ ሆነው
በጎበኙበት ወቅት የተሸለሙት ነው፡፡ “የለውጥ ሐዋሪያ በመሆን ላበረከቱት አስተዋጽኦ የተሰጠዎት የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ነው!”
ነበር ያሉት የወቅቱ የካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ቻንስለር፡፡
2ኛ. ከአቴንስ ዩኒቨርሲቲ - ካፖዲስትሪያን ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና የክብር ዲግሪ፣ በሚያዝያ
26 ቀን 1946 ዓ.ም ነበር፡፡ የሸላሚው ዩኒቨርሲቲ ተወካይ፣ “የሀገራቸውን ዕድገትና እድገት ስላስጠበቁና የነፃነት ፋና በርቶ
እንዲኖር ስለሰሩ ይህ ዲግሪ ተሰጥቷቸዋል፤” ይላል፡፡
3ኛ. ከሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ - የሕግ የክብር ዶክትሬት
ዲግሪ ሲሆን በግንቦት 20 ቀን 1946 ዓ.ም ነበር የተሰጣቸው፡፡ “በሰላማዊ ዘዴ ለሀገርዎት የባሕር በር ስላስከፈቱላትና፣
የወጪና ገቢ ንግድ አራት እጥፍ እንዲያድግ ስላደረጉ” ነበር የዩኒቨርሲቲው ተወካይ ያሉት፡፡

5ኛ. ከሞንትሪያል ዩኒቨርሲቲ - በፖለቲካ ጥበብ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ የተሰጣቸው ሲሆን፣ በግንቦት
28 ቀን 1947 ዓ.ም ነው፡፡ “በ1933 ዓ.ም ወደመናገሻ ከተማዎ በተመለሱበት ወቅት በቀልንና ጭካኔን ወደኋላ በማድረግ አዲሲቷን
ኢትዮጵያን በአስተዋይነት ስለመሩ፣ ይህ የክብር ዶከትሬት ዲግሪ ተሰጥቶዎታል፤” ይላል፡፡
6ኛ. ከመክሚል ዩኒቨርሲቲ - የሕግ የክብር ዶክትሬት
ዲግሪ ሲሆን በ1946 ዓ.ም ነው፡፡ “ለኢትዮጵያ ልጆች ትምህርት በሰፊው እንዲዳረስና ዕውቀት እንዲስፋፋ ስለሠሩ፣ ይህ የክብር
ዲግሪ ተሰጥቶዎታል” ይላል፡፡
7ኛ. ከሚቺጋን ዩኒቨርሲቲ - የሕግ የክብር ዶክትሬት
ዲግሪ ሲሆን፣ ዕለቱ ግንቦት 30 ቀን 1946 ዓ.ም ነበር፡፡ የዩኒቨርሲቲው ተወካይ እንዳሉት ከሆነ፣ “ስለግርማዊነትዎ ታላቅ
ሰብዕና የተሰጠ የክብር መግለጫ ነው፡፡”
8ኛ. ከኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የተሰጣቸው - የሕግ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሲሆን፣ ዕለቱም ጥቅምት
10 ቀን 1947 ዓ.ም ነበር፡፡ “የሀገርዎትን የኢትዮጵያን ነፃነትና ሉዓላዊነት በበሳል አካሄድ ስላስመለሱ፣ የኢትዮጵያን ባሕልና
እምነት በሰላማዊ መንገድ ስላሻሻሉና ስላጸኑ የተሰጠዎት የክብር ማዕረግ ነው፣” ይላል፡፡
9ኛ. ከቦን ዩኒቨርሲቲ የተሰጠ - የሳይንስ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሲሆን፣ ሰጪው ጥቅምት 25 ቀን 1947
ዓ.ም ነበር የሸለማቸው፡፡ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንትም፣ “በኢትዮጵያ ውስጥ ለእርሻ መስፋፋትና እድገት ከቀድሞ ጀምሮ ለፈጸሙት ከፍተኛ
ተግባር የተሰጠዎት የክብር መግለጫ ነው፤” ይላል፡፡
10ኛ. ከባናራስ ዩኒቭረሲቲ የተሰጠ - የሥነ-ጽሑፍ የክብር
ዶክትሬት ዲግሪ ሲሆን በሕዳር 4 ቀን 1949 ዓ.ም ነበር፡፡ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት እንደተናገሩት ከሆነ፣ “ግርማዊነትዎ፣
እርስዎ የኢትዮጵያን የሚመሩ ዋና መሀንዲስና የነፃነቷም ዋና ጠበቃ በመሆንዎት ይህ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ተሰጥቶዎታል፤” ይላል፡፡
11ኛ. ከሞስኮ ዩኒቨርሲቲ የተሰጣቸው - የሕግ የክብር
ዶክትሬት ዲግሪ ሲሆን፣ ዕለቱም ሐምሌ 5 ቀን 1951 ዓ.ም ነበር፡፡ የዩኒቨርሲተው ፕሬዝዳንት ስለሽልማቱ እንዲህ ሲሉ ነበር
የገለጡት፤ “በርዕዮተ-ዓለም መለያየትንና ጎራ ለይቶ መፋለምን ወደኋላ በማለት፣ በሰላም አብሮ ስለመኖር ያለዎትን መንፈስ በታላቅ
አድናቆት ተመልክተነዋል፡፡ ስለዚህም ይህ ክብር ይገባዎታል፤” ነበር ያሉት፡፡
12ኛ. ከቻርልስ ዩኒቨርሲቲ የተሰጠ - የሕግ የክብር
ዶክትሬት ዲግሪ ሲሆን፣ ቀኑም በሐምሌ 8/1951 ዓ.ም ነው፡፡ ክብሩም የተሰጣቸው፣ “የኢትዮጵያን ነፃነት ከአጠቂ ጠላት
በመከላከላቸውና ነፃ በማጣታቸው፤” እንደሆነ ይገልጻል፡፡
13ኛ. ከጆርጅ ታውን ዩኒቨርሲቲ የተሰጣቸው - በሥነ-ጽሑፍ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሲሆን፣ በመስከረም 22 ቀን 1956 ዓ.ም ነበር፡፡
የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት እንዳስታወቁት ከሆነ፣ “ለሀገርዎት ህዝብ ስልጣኔና ስለአፍሪካም ነፃነት ትግል ከፍ ያለ ተጋድሎ በማድረግዎት
የተሰጠዎት ሽልማት ነው፤” ይላል፡፡
14ኛ. ከላይቤሪያ ዩኒቨርሲቲ የተሰጣቸው - የሕግ የክብር
ዶክትሬት ዲግሪ ሲሆን፣ በኅዳር 27 ቀን 1956 ዓ.ም ነበር፡፡ “የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እንዲቋቋም በብርቱ ስለሰሩና
የድርጅቱም የመጀመሪያው ሊቀ-መንበር ሆነው ስላገለገሉ የተሰጠዎት የክብር መግለጫ ነው፤” ይላል፡፡
15ኛ. ከአሜሪካን ፖሊካልቸራል ዩኒቨርሲቲ የተሰጣቸው - የዩኒቨርሲተው የበላይ ጠባቂነት
የክብር ዶክትሬት ዲግሪና ሊቀመንበርነት ማዕረግ ነው፡፡ “ለዕውቀት መስፋፋት ተግተው ስለሠሩ፣ በበላይ ጠባቂነት እንዲሰሩልን
ሾመንዎታል፤” ነበር የሚለው፡፡
16ኛ. የሩማንያ ብሔራዊ ዩኒቨርሲቲ፤ 17ኛ. የቡልጋሪያና 18ኛም የግሪክ ብሔራዊ ዩኒቨርሲቲዎች ሦስቱም በ1957 ዓ.ም
በየሕግ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሰጥተዋቸዋል፡፡
19ኛ. ከሞርሐውስ ኮሌጅ - በሕግ የክብር የዶክትሬት
ዲግሪ ሲሰጣቸው፣ ቀኑም ሐምሌ 4 ቀን 1961 ዓ.ም ነው፡፡ የኮሌጁ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሁባ ኤም ግሎስተር እንዳሉት ከሆነ፣ “ግርማዊነትዎ
ባሳዩት ፍጹም የመሪነትና ባሳዩት ታላቅ ሰውነት ስለፈጸሟቸው ተግባሮች፣ ይህን ዲግሪ በመስጠት ኮሌጁ ለርስዎ ያለውን አክብሮት ይገልጻል፤”
ነበር ያሉት፡፡ (አዲስ ዘመን፣ ሐምሌ 5 ቀን 1961 ዓ.ም. ገጽ 1 ላይ)፡፡
20ኛ. ከለንደን ዩኒቨርሲቲ - በፖለቲካ ሳይንስ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ የተሰጣቸው ሲሆን እለቱም ሰኔ 15 ቀን
1964 ዓ.ም ነው፡፡ እንዲሁም፣ የእንግሊዝ ንግስት ኤልሳቤጥ በዕለቱ፣ “በልበሙሉነትና በቆራጥነት ላሳዩት አመራር The
Knight of Garter የተባለውን የክብር ከፍተኛ ማዕረግ ሸልመዋቸዋል፡፡ (አዲስ ዘመን፣ ሰኔ 23 ቀን 1964 ዓ.ም፣ ገጽ 3 ላይ ተመልከት፡፡)
21ኛ. የቫቲካን ዩኒቨርሲቲ - በፖለቲካ ሳይንስ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ፣ በነሐሴ 1964 ዓ.ም ሰጥቷቸዋል፤ (መነን፣
ነሐሴ 1964 ዓ.ም እትም)
በአጠቃላይ ሲታይ አስራ ሦስት የሕግ የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎችን ሲያገኙ፣ ሁለት በሥነ-ጽሑፍ፣ አንድ በፍልስፍና፣ ሦስት
በፖለቲካ ሳይንስ፣ አንድ በሳይንስ፣ አንድ የበላይ ጠባቂነት ዲግሪዎችን አግኝተዋል፡፡ በሃምሳ አመታት ለኢትዮጵያ ሕዝብና ለአፍሪካ
እንዲሁም ለዓለም ሰላም ባደረጉት የስራ-ጥረት እነዚህን የክብር ማዕረጎች ለማግኘት ችለዋል፡፡ እንኳን በኢትዮጵያ፣ በአፍረካም ቢሆን የሚተካከላችው የደቡብ አፍሪካው ስመ-ጥሩ መሪ ኔልሰን
ማንዴላ ብቻ ነው፡፡ ከሃያ ሰባት በላይ የክብር ዶክትሬቶችን አግኝቷል፡፡
ለማጠቃለል ያህል፣ አቶ መለስ ዜናዊ በአንድ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሲከተሉ፣ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በሃያ አንድ
የክብር ዶክትሬት ዲግሪዎች በሰፊ ልዩነት ይመራሉ፡፡ ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያምም በምንም ነጥብ ጭራ ሆነው ይከተላሉ፡፡ የመሪዎቹ
የክብር ዶክትሬት መጠን መለያየት በዋናነት የሚያሳየው፣ የመሪዎቹን በብሔራዊና በዓለም-ዓቀፍ ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ተቀባይነትና
ተሰሚነትም ጭምር ነው፡፡ ግርማዊ ጃንሆይ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በሃያ አንድ ጊዜ (እጥፍ ድርብ) ተቀባይነትና ተደማጭነት
ነበራቸው ማለት ይቻል ይሆን? ጃንሆይ፣ አፍኖ የገደላቸውን ኮሎኔል መንግስቱን ሃያ አንድ ለምንም ይመሩታል፡፡ አቶ ኃይለማርያም
ደሳለኝስ ቀዳሚዎቻቸውን በስንት የክብር ዶክተሬት ዲግሪዎች ይቀድሙ ወይም ይከተሉ ይሆን? ሁሉንም እናይ ዘንድ፣ የዚያ ሰው ይበለን!
ይህን ታሪካዊ መረጃ ስላካፈሉን ከልብ አመሰግናለሁ። እግዚአብሔር ይስጥልኝ።
ምላሽ ይስጡሰርዝ